በጋዛ በተፈጸመ አዲስ ጥቃት በርካታ ፍልስጤማውያን መገደላቸው ተነገረ
አቅራቢ ዘላለም ኃይሉ ፥ አዲስ አበባ
የጋዛ የጤና ሚኒስቴር ባለስልጣናት እንዳስታወቁት የእስራኤል ወታደሮች የተፈናቀሉ ሰላማዊ ሰዎች በተጠለሉባቸው ቦታዎች ላይ በማነጣጠር በ24 ሰዓታት ውስጥ በጋዛ ዙሪያ በፈፀሙት የአየር ድብደባ በትንሹ 81 ፍልስጤማውያን መገደላቸውን ይፋ አድርገዋል።
ጥቃቱ በጋዛ ከተማ በሚገኘው ስታዲየም አቅራቢያ በሚገኝ የተፈናቃዮች ካምፕ እና በቱፋ ሰፈር በሚገኝ ትምህርት ቤት ላይ መፈጸሙን ባለስልጣናቱ የገለጹ ሲሆን፥ ከሟቾቹ መካከል ህፃናትን ጨምሮ የአንድ ቤተሰብ ሙሉ አባላት እንደተገደሉ ተገልጿል።
የጋዛ ጤና ጥበቃ ሚኒስቴር ጦርነቱ ከጀመረበት መስከረም 26 ቀን 2017 ዓ.ም. ጊዜ አንስቶ ከ56,400 በላይ ፍልስጤማውያን መገደላቸውን ያመላከተ ሲሆን፥ የጉዳቱ መጠን ከጊዜ ወደ ጊዜ መጨመር የዩናይትድ ስቴትስ እና የኳታር ዲፕሎማሲያዊ ጥረቶች ጨምሮ ዸም አቀፍ የተኩስ አቁም ጥሪ ተጠናክሮ እንዲቀጥል ማድረጉ ተነግሯል።
የእስራኤል ጦር የሃማስ መስራች አባላት ውስጥ አንዱ የሆነውን ግለሰብ መግደሉን ያሳወቀ ሲሆን፥ እስራኤል በጋዛ መጋቢት ወር መጀመሪያ ላይ የጀመረችውን መጠነ ሰፊ ወታደራዊ ዘመቻዋን አጠናክራ በመቀጠል፥ ከዚያን ጊዜ ጀምሮ ቢያንስ 6,050 ፍልስጤማውያን መገደላቸው እና ከ21,000 በላይ መቁሰላቸው የተገለጸ ሲሆን፥ ይህም ጦርነቱ ከተጀመረበት ጊዜ አንስቶ የቆሰሉትን አጠቃላይ የጉዳት መጠን ከ133,000 በላይ ማድረሱን በአከባቢው የሚገኙ ባለስልጣናት ገልጸዋል።
የኢራን የዩራኒየም ማበልጸጊያ ፕሮግራም
በሌላ ዜና የተባበሩት መንግስታት የኒውክሌር ጦር መሳሪያ ቁጥጥር ቢሮ ሃላፊ ኢራን በወራት ውስጥ ዩራኒየምን ማበልፀጓን ልትቀጥል ትችላለች ብለዋል።
የዸም አቀፉ የአቶሚክ ኢነርጂ ኤጀንሲ ዋና ዳይሬክተር ራፋኤል ግሮስሲ በበኩላቸው ባለፈው ሳምንት የተፈፀመው የአየር ድብደባ የኑክሌር መሠረተ ልማቶችን ቢጎዳም ሙሉ ለሙሉ በሚባል ደረጃ አለማውደሙን የገለጹ ሲሆን፥ የግሮሲ አስተያየቶች የኢራን የኒውክሌር አቅም በከፍተኛ ሁኔታ ተዳክሟል የሚለውን የአሜሪካ አባባል የሚቃረን እንደሆነ ተገልጿል።