የኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ልኡካን የቅዱሳን ጴጥሮስ እና ጳውሎስ በዓል በጋራ ለማክበር ወደ ሮም መጥተዋል
የዚህ ዝግጅት አቅራቢ ዮሐንስ መኰንን - ቫቲካን
የቁስጥንጥንያ ፓትርያርክ ጽሕፈት ቤት የክርስቲያኖች አንድነት ልዑካን ቡድን ከዓርብ ሰኔ 20 እስከ እሑድ ሰኔ 22/2017 ዓ. ም. ሮምን እየጎበኘ መሆኑን የቅድስት መንበር መግለጫ ክፍል ዓርብ ዕለት ባወጣው መግለጫ አስታውቋል።
የልዑካን ቡድኑ ጉብኝት ሁለቱ አብያተ ክርስቲያናት የባልደረቦቻቸውን ማለትም በካቶሊካዊት ቤተ ክርስቲያን በየዓመቱ ሰኔ 22 የሚከበረውን የቅዱሳን ጴጥሮስ እና ጳውሎስ፣ በኢስታንቡልም በየዓመቱ ኅዳር 21 የሚከበረውን የሐዋርያው ቅዱስ እንድርያስ ዓመታዊ በዓል ልማዳዊ አከባበር ልውውጥ መሠረት በማድረግ እንደሆነ ታውቋል።
የኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ልኡካን ቡድንን የመሩት የኬልቄዶኒያ ሊቀ ጳጳስ ብጹዕ አቡነ አማኑኤል በፓትርያርክ ጽሕፈት ቤት የካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን ሲኖዶሳዊ ግንኙነት ኮሚሽን ፕሬዝዳንት እንደሆኑ ታውቋል።
ወደ ሮም የተጓዙት ሊቀ ጳጳስ ብጹዕ አቡነ አማኑኤል የፓትርያርክ ብጹዕ ወቅዱስ በርተሎሜዎስ ቀዳማዊ ልኡክ በመሆን ሲሆኑ በበዓሉ ላይ ከአባ ኤቲዮስ እና ከአባ ኢሮኒሞስ ጋር አብረው እንደሚገኙ ታውቋል።
ልዑካኑ እሑድ ሰኔ 22/2017 ዓ. ም. በሚከበረው የቅዱሳን ጴጥሮስ እና ጳውሎስ ዓመታዊ በዓል ላይ ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ 14ኛ በሚመሩት የመስዋዕተ ቅዳሴ ሥነ-ሥርዓት ላይ የሚገኙ ሲሆን በዋዜማው ማለትም ቅዳሜ ሰኔ 21/2017 ዓ. ም. ከርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ አሥራ አራተኛ ጋር ተገናኝተዋል።