MAP

ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ የመልአከ እግዚአብሔር ጸሎትን የመሩበት ሥነ-ሥርዓት ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ የመልአከ እግዚአብሔር ጸሎትን የመሩበት ሥነ-ሥርዓት   (@VATICAN MEDIA)

ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ “እራሳችንን ለግጭት እና ለጦር መሣሪያዎች ማንበርከክ የለብንም” ሲሉ አሳሰቡ

ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ አሥራ አራተኛ፥ በላቲን የአምልኮ ሥርዓት መሠረት ዓርብ ነሐሴ 9/2017 ዓ. ም. የተከበረውን የፍልሰታ ማርያም በዓል በማስመልከት ቃለ ምዕዳን አሰምተዋል። በዕለቱ ከምዕመናኑ ጋር ሆነው የመልአከ እግዚአብሔር ጸሎት ያደረሱ ሲሆን፥ ቀጥለውም ባለፉት ዘመናት የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ሚና ለሰዎች በሰጠው ተስፋ ላይ በማሰላሰል ንግግር አድርገዋል። በዚህ ንግግራቸውም ሁሉም ሰው በአመጽ መካከል ተስፋን ሊያጣ እንደማይገባ አሳስበዋል።

የዚህ ዝግጅት አቅራቢ ዮሐንስ መኰንን - ቫቲካን

በካስቴል ጋንዶልፎ የርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ማረፊያቸው ካቀረቡት የመልአከ እግዚአብሔር ጸሎት ቀጥለው በሥፍራው ለተገኙት ምዕመናን የፍልሰታ ማርያም በዓልን በማስመልከት ንግግር ባሰሙበት ወቅት፥ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ሰላምን እንድታማልደን ጸሎታቸውን አድርሰው፥ “እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በልጆቿ በተለይም በሕፃናት እና በአቅመ ደካሞች ላይ በሚደርስ መከራ ትሰቃያለች” ብለው፥ “ባለፉት ዘመናት በሙሉ ለተቸገሩት ሰዎች ያላትን ቅርበት በመልዕክቶቿ እና በግልጸቷ አረጋግጣለች” ብለዋል።

ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፒዮስ 12ኛ፥
ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፒዮስ 12ኛ፥

የቀድሞው ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፒዮስ 12ኛ፥ “በዓለም ታይቶ የማያውቅ ደም አፋሳሽ ሁለተኛው የዓለም ጦርነት” በማለት እንደ ጎርጎሮሳውያኑ በ1950 ዓ. ም. የፍልሰታ ማርያም ዶግማ ማወጃቸው የሚታወስ ሲሆን፥ በመልዕክታቸውም፥ “በእመቤታችን ማርያም ክቡር ምሳሌ ላይ የሚያሰላስሉት በሙሉ በሰው ሕይወት ዋጋ ይበልጥ እርግጠኞች ይሆናሉ ብለን ተስፋ የምናደርግበት ምክንያት አለ” ካሉ በኋላ በመቀጠልም ዓለም በጦርነት ምክንያት የሚታረደውን የሰውን ሥጋ ዳግም እንደማያይ ያላቸውን ተስፋ ገልጸዋል።


ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ አሥራ አራተኛ፥ የቀድሞው ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት የተናገሯቸው ቃላት ዛሬም ጠቃሚ ሆነው ይቀጥላሉ በማለት አበክረው ተናግረው፥ የሰው ልጆች በሙሉ በዓለም ላይ እየተስፋፋ በመጣ ዓመፅ መካከል አቅመ ቢስነት እንደሚሰማቸው እና በአመጹ መብዛት ምክንያት ማንኛውም ዓይነት የሰው ልጅ የሰላም ጥረት ተቀባይነትን ወደማያገኝበት ደረጃ ላይ ደርሷል” ብለዋል።

ርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ በንግግራቸው ማጠቃለያ ባቀረቡት ማሳሰቢያ፥ “ነገር ግን ተስፋ ማጣት የለብንም” ብለው፥ እግዚአብሔር ከሰው ልጆች ኃጢአት እና ከሚደርስባቸው ግፎች በሙሉ እንደሚበልጥ ተናግረው፥ “እራሳችንን ለግጭት እና ለጦር መሣሪያዎች የበላይነት ማንበርከክ የለብንም፤ ምክንያቱም እግዚአብሔር አምላካችን ከእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ጋር እንደሚረዳን እናውቃለን፤ የሰላሙን መንገድ እንደገና ማግኘት የምንችለውም በእግዚአብሔር ምሕረት ብቻ ነው” ሲሉ አስረድተዋል።

16 Aug 2025, 10:18