ብፁዕ ካርዲናል ፋረል የርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስን ሞት በይፋ አረጋግጠዋል!
የዚህ ዝግጅት አቅራቢ መብራቱ ኃ/ጊዮርጊስ-ቫቲካን
ሰኞ ሚያዝያ 13/2017 ዓ.ም በሮ የሰዓት አቆጣጠር ከቀኑ 8፡00 ሰዓት ላይ የቅድስት ሮማዊ ቤተ ክርስቲያን ካሜርሌንጎ ብፁዕ ካርዲናል ኬቨን ፋሬል የሟቹን የርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስን አስከሬን በሬሳ ሣጥን ውስጥ የማስቀመጥ ሥነ-ሥርዓት መርተዋል። በቫቲካን በሚገኘው የቅድስት ማርታ የጸሎት ቤት ሥነ-ሥርዓት ተፈጽሟል።
በሥፍራው የተገኙት የብፁዕን ካርዲናሎች የመማክርት ቡድን ዋና ጸኃፊ ብፁዕ ካርዲናል ጆቫኒ ባቲስታ ሬ እና የሟቹ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ ቤተሰብ አባላት ከዶ/ር አንድሪያ አርካንጄሊ፣ የጤና እና ንጽህና ዳይሬክቶሬት ምክትል ዳይሬክተር ዶ/ር ሉዊጂ ካርቦን ጋር በቅደም ተከተል ተገኝተዋል።
ከስርአቱ በኋላ የቫቲካን ግዛት የጤና እና ንፅህና ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር ዶ/ር አንድሪያ አርካንጄሊ እንዳረጋገጡት ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት በስትሮክ (በአንጎል ውስጥ የደም ዝውውር መቋረጥ፣ ወይም መጓጎል) ምክንያት ሕይወታቸው ያለፈ ሲሆን ይህም ለኮማ እና ሊቀለበስ የማይችል የልብና የደም ዝውውር ውድቀት ወይም መስተጓጎል ምክንያት ሆኗል።
እንደ የሕክምና ዘገባው፣ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳቱ በብዙ ተህዋሲያን የሁለትዮሽ የሳንባ ምች፣ በርካታ ብሮንካይተስ፣ የደም ግፊት እና ዓይነት ሁለት የስኳር በሽታ ሳቢያ የሚከሰቱ አጣዳፊ የመተንፈሻ አካላት ችግር ቀደም ብለው ነበራቸው።