ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ በዓለም ዙሪያ ባሉ የግጭት ቀጠናዎች ሰላም እንዲሰፍን ጸልዩ!
የዚህ ዜና አቅራቢ መብራቱ ኃ/ጊዮርጊስ-ቫቲካን
በቅዱስ ጴጥሮስ አደባባይ በርዕሠ ሊቃነ ጳጳሳት ፍራንችስኮስ የተመራው የመከላከያ ሠራዊት፣ የፖሊስና የደኅንነት አባላት የኢዮቤልዩ ቅዳሴ ማጠቃለያ ላይ፣ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳቱ ከሁለተኛው የቫቲካን ጉባኤ ሰነድ “Gaudium et spes” በመጥቀስ እነዚህ ኃይላት ለሰላም መስፈን የበኩላቸውን አስተዋጽኦ ማበርከት ያለውን ጠቀሜታ ገልጸዋል።
በመጀመሪያ በዚህ የኢዮቤልዩ በዓል ላይ የተገኙትን፣ ለእነዚህ አካላት የሐዋርያዊ አገልግሎት የሚሰጡትን ካህናት ጨምሮ ለሁሉም ሞቅ ያለ ሰላምታ ቅዱስነታቸው አቅርበዋል፣ እናም በዓለም ዙሪያ በውትድርና አገልግሎት ላይ ለሚገኙ ሰዎች ሁሉ ሰላምታቸውን አቅርበዋል።
በላቲን ቋንቋ "Gaudium et spes” የተሰኘውን የሁለተኛው የቫቲካን ጉባኤ ሰነድ በማስታወስ አበረታቷቸዋል፣ “ለአገራቸው ወታደራዊ አገልግሎት ራሳቸውን የሚሠጡ ሰዎች ራሳቸውን የጸጥታና የሕዝቦች ነፃነት ወኪሎች አድርገው ሊቆጥሩ ይገባል” ብለዋል። የትጥቅ አገልግሎቱን “ራስን ለመከላከል ብቻ፣ በሌሎች አገሮች ላይ የበላይነትን ላለመጫን፣ ሁልጊዜም ግጭቶችን በሚመለከት ዓለም አቀፍ ስምምነቶችን በማክበር እና ከሁሉም በላይ ለሕይወትና ለፍጥረት የተቀደሰ አክብሮት” መሆኑን ጠቁመዋል።
በማጠቃለያው ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳቱ ሁሉም ሰው "በተሰቃየችው" ዩክሬን ፣ ፍልስጤም ፣ እስራኤል እና በመካከለኛው ምስራቅ ፣ በማይናማር ፣ ኪቩ (ዲሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ) እና በሱዳን ሰላም እንዲሰፍን እንዲጸልዩ ቅዱስነታቸው ጠይቀዋል። "መሳሪያዎች በየቦታው ጸጥ እንዲሉ" እና "የሰላም ጥያቄ የሚጠይቁ ሰዎች ጩኸት እንዲሰማ" ቅዱስነታቸው ተመጽነዋል። ግጭት ባለባቸው ስፍራዎች በሙሉ ሰላም እንዲሰፍን "ጸሎታችንን የሰላም ንግሥት ወደ ሆነችው ድንግል ማርያም አማላጅነት እናቀርባለን" ካሉ በኋላ ቅዱስነታቸው መልእክታቸውን ደምድመዋል።