MAP

ሃምሌ 10 ቀን 2017 ዓ.ም. ጥቃት የደረሰበት በጋዛ ውስጥ የሚገኘው የቅድስት ቤተሰብ ካቶሊካዊት ቤተክርስቲያን ሃምሌ 10 ቀን 2017 ዓ.ም. ጥቃት የደረሰበት በጋዛ ውስጥ የሚገኘው የቅድስት ቤተሰብ ካቶሊካዊት ቤተክርስቲያን   (AFP or licensors)

አባ ሮማኔሊ በጋዛ የሚገኘው የካቶሊክ ደብር እስራኤል ባስተላለፈችው ለቆ የመውጣት ትእዛዝ ሥር እንዳልገባ አሳወቁ

የጋዛ የቅድስት ቤተሰብ ካቶሊካዊት ቤተ ክርስቲያን ደብር ካህን የሆኑት አባ ገብርኤል ሮማኔሊ ለቫቲካን መገናኛ ብዙኃን እንደተናገሩት በጋዛ ከተማ የሚገኘው ብቸኛው የካቶሊክ ቤተክርስቲያን እና አከባቢው እስራኤል ባስተላለፈችው ለቆ የመውጣት ትእዛዝ ሥር እንዳልሆነ ገልጸው፥ ሁሉም ሰው ለሰላም እንዲጸልይ በድጋሚ ጥሪያቸውን አቅርበዋል።

  አቅራቢ ዘላለም ኃይሉ ፥ አዲስ አበባ

“በቤተክርስቲያናችን እና በአቅራቢያው ምንም አይነት የመልቀቂያ ትእዛዝ አልተላለፈም” ያሉት አባ ገብርኤል፥ አካባቢው በአሮጌው የጋዛ ከተማ በትልቁ የዘይቱን ሰፈር ውስጥ እንደሚገኝ አስረድተዋል።

በጋዛ የሚገኘው የካቶሊክ ቤተክርስቲያን የቅድስት ቤተሰብ አጥቢያ ካህን የሆኑት አባ ገብርኤል ሮማኔሊ ማክሰኞ ነሐሴ 13 ቀን 2017 ዓ.ም. ለቫቲካን መገናኛ ብዙኃን በሰጡት መግለጫ አካባቢው አደገኛ እና ሌት ተቀን ለቤተክርስቲያኑ በቅርብ ርቀት፣ አንዳንዴም ከሩቅ አከባቢ የቦምብ ፍንዳታ እንደሚሰማ ጠቅሰው፥ አንዳንድ ጊዜ ደግሞ የቦንብ ፍንጣሪዎች ሳይቀሩ አከባቢያቸው ላይ እንደሚወድቁ አስረድተዋል።

እንደ አለመታደል ሆኖ ጦርነቱ በተጠናከረ ሁኔታ መቀጠሉን የገለጹት ካህኑ፥ በየቀኑ የሚሞቱ፣ የሚቆስሉ እና የውድመቱ ቁጥር እየጨመረ መምጣቱን ገልጸው፥ በዚህም ምክንያት አጠቃላይ የሲቪሉ የጋዛ ህዝብ ፍላጎት በየዕለቱ ከፍ እንደሚል በመጠቆም፥ “ሆኖም ግን እግዚአብሔር ይመስገን ደህና ነን” ካሉ በኋላ “ስለ ሰላም መጸለያችንን አጠናክረን እንቀጥላለን” በማለት ደምድመዋል።

ጦርነቱ ከተቀሰቀሰበት መስከረም 26 ቀን 2016 ዓ.ም. ጀምሮ በመቶዎች የሚቆጠሩ በርካታ ሰዎች በጋዛ በምትገኘው ብቸኛዋ የካቶሊክ ቤተክርስቲያን ተጠልለው እንደሚገኙ የሚታወቅ ሲሆን፥ ሃምሌ 10 በቤተክርስቲያኑ አቅራቢያ በደረሰው የታንክ ጥቃት ሶስት ሰዎች መሞታቸው እና በርካቶች ደግሞ መቁሰላቸውን እንዲሁም አባ ሮማኔሊ እግራቸው በአደጋው መቁሰሉ ይታወሳል።

ይህ ጥቃት በደረሰበት ወቅት ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ሊዮ አሥራ አራተኛ ‘አስከፊው ጦርነት’ በአስቸኳይ እንዲቆም ጥሪ ካቀረቡ በኋላ፥ ግጭቱ በሰላማዊ መንገድ እንደሚፈታ ያላቸውን ተስፋ በመግለጽ ለተጎጂዎች መጸለያቸው ይታወሳል።

20 Aug 2025, 13:57